የኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን ወክለው በውጭ ሀገር ያሉ ሊቃነ ጳጳሳት ለጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ወደ ሀገር ቤት እንዲመጡ የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ እንደተላከላቸው ታውቋል።
በዓመት ሁለት ጊዜ የሚደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ላይ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ቤተ ክርስቲያንን ወክለው ሀገረስብከት የሚያሰተዳድሩ ሊቃነ ጳጳሳት ከአቅም በላይ ካልሆነ በስተቀር በአካል መገኘት አለባቸው።ነገር ግን የተወሰኑት ሊቃነ ጳጳሳት ባልታወቀ ምክንያት ባለፉት አራት እና አምስት ዓመታት በጉባኤው ያልተገኙ መሆኑ ግራ የሚያጋባ ጉዳይ ሆኖአል። በተለይም በአሜሪካን ሀገር ያሉት ብፁዕ አቡነ አብረሃም እና አቡነ ኤዎስጣቲዎስ እንዲሁም በሰሜን ምዕራብ አውሮፓ የሚገኙት ብፁዕ አቡነ እንጦንስ አዲስ አበባ በሚደረገው ርክበ ካህናት ጉባኤ ከተሳተፉ አምስተኛ ዓመታቸው ሲሆን ግንኙነታቸው በስልክ እና በፋክስ ቢቻ መሆኑን ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል።
ወደ ሀገር ቤት ለመሄድ ያለመፈለጋቸው ጉዳይ እቀየራለሁ ከሚል ስጋት እንደሆነ ብዙዎች ይስማማሉ ባለፈው ዓመት አቡነ አብረሃም በሌሉበት ከቦታቸው እንዲነሱ ሲወሰን በሰሜን አሜሪካ ያሉ ምዕመናን ባሰሙት ተቃውሞ እንዲቀጥሉ መደረጉ ይታወሳል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ለጥቅምት 2004 ዓ፡ም የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ሁሉም ከያሉበት እንዲመጡ ትዕዛዝ የተላለፈ ሲሆን በተለይም ከላይ ለተጠቀሱ አባቶች ጥብቅ ማሳሰቢያ እንደደረሳቸው ለማወቅ ችለናል::አባቶችም የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ ባንድነት ለመምከር እንደሚመጡ ይጠበቃል።
ቤተ ክርስቲያናችንን አምላክ ይጠብቅልን አሜን!!!
ReplyDelete